ቀጥታ, ኢራን ለአሜሪካ አዲስ የሰላም ዕቅድ በፓኪስታን በኩል ማቅረቧ ተነገረ

በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደውን ጦርነት ያስቆማል የተባለ ኢራን ያቀረበችውን አዲስ ዕቅድ ፓኪስታን ለአሜሪካ መስጠቷን ምንጮች ለሮይተርስ ተናገሩ። በሁለቱ አገራት መካከል እየተካሄደ ያለው የሰላም ድርድር ውጤት ሳያስገኝ በእንጥልጥል ባለበት ወቅት ዛሬ ሰኞ ነው ፓኪስታን የኢራንን አዲስ ዕቅድ ለአሜሪካ ያቀረበችው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኬንያ የነዳጅ ዋጋ መጨመርን በመቃወም አደባባይ የወጡ ከ200 በላይ ሰዎች በቁጥጥር ሥር ዋሉ

    የኬንያ ፖሊስ የነዳጅ ዋጋ መጨመርን በመቃወም አደባባይ ከወጡ መካከል ከ200 በላይ ሰዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን አስታወቀ።

    የናይሮቢ ከተማ ፖሊስ አዛዥ ኢሳ ሞሐሙድ በመላ አገሪቱ የተጠራን የትራንስፖርት ማቆም አድማን ተከትሎ ለተቃውሞ አደባባይ ከወጡ ሰዎች መካከል 225ቱ በቁጥጥር ሥር ውለዋል ብለዋል።

    በኬንያ ዛሬ ሰኞ ግንቦት 10 2018 ዓ.ም. ከፍተኛ የነዳጅ ጭማሪን በመቃወም በመላ አገሪቱ የመጓጓዣ አገልግሎት ሰጪዎች ሥራ አቁመው ውለዋል።

    በናይሮቢ እና በዋና ዋና ከተማዎች የአውቶቡስ፣ የሞተር ሳይክል እና ሚኒባስ ትራንስፖርት አገልግሎት በመቋረጡ ተጠቃሚዎች ረዥም ርቀት በእግራቸው ለመጓዝ ተገድደዋል።

    በአንዳንድ አካባቢዎች ተቃዋሚ ሠልፈኞች መንገድ ዘግተው ጎማ ሲያቃጥሉ ታይተዋል።

    ፖሊስ መንገዶችን ለመክፈት በሚሞክርበት ወቅት ከተቃዋሚ ሠልፈኞቹ ጋር የተጋጨ ሲሆን ለመበተን አስለቃሽ ጋዝ ተጠቅሟል።

    የናይሮቢ ፖሊስ አዛዥ አምስት የፖሊስ እና አንድ የግለሰብ መኪኖች በሠልፈኞቹ መውደማቸውን አስታውቀዋል።

    እስካሁን ድረስ በተቃውሞ ሠልፉ ምክንያት የሞተ ሰው ስለመኖሩ የተባለ ነገር የለም።

    ባለፈው ሳምንት የኬንያ ኢነርጂ እና ፔትሮሊየም ቁጥጥር ባለሥልጣን በመካከለኛው ምሥራቅ ያለውን ውጥረት በመጥቀስ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ ይፋ ካደረገ በኋላ ተቃውሞ ተቀስቅሷል።

    የትራንስፖርት አገልግሎት አቅራቢዎች በተለይ ደግሞ የሕዝብ ማመላለሻ ባለንብረቶች እና አሽከርካሪዎች የዋጋ ጭማሪው ለመስራት አስቸጋሪ እንዳደረገባቸው ተናግረዋል።

    በተቃውሞ ምክንያት በርካታ የረዥም ርቀት ተጓዥ አውቶብሶች ጉዟቸውን በመሰረዛቸው የተነሳ መንገደኞች ተጉላልተዋል።

    ዛሬ በኬንያ በነበረው የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት አቅራቢዎች ተቃውሞ የተነሳ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም የንግድ ተቋማት ተዘግተው ውለዋል።

    የአገሪቱ ገንዘብ ሚኒስትር ጆን ምባዲ የዓለም አቀፍ ነዳጅ ዋጋ ንረት በመካከለኛው ምሥራቅ ካለው ጦርነት ጋር እንደሚያያዝ ጠቅሰው ይህም በአገሪቱ ለተከሰተው ጭማሪ ምክንያት መሆኑን ተናግረዋል።

    የዓለም የነዳጅ ዋጋ በዚሁ ከቀጠለ መንግሥት የታክስ እፎይታን ከግምት ሊያስገባ እንደሚችል ጨምረው አስታውቀዋል።

    የትራንስፖርት አገልግሎት አቅራቢዎች እና የተሽከርካሪ ባለቤቶች መንግሥት የነዳጅ ዋጋ እንዲቀንስ ቢጠይቁም እስካሁን ድረስ ይህ ነው የሚባል መግባባት ላይ አልደረሱም።

  2. አሜሪካ ለወታደራዊ እርምጃ “ሐሰተኛ ምክንያቶችን” እያደራጀች ነው ስትል ኩባ ከሰሰች

    የኩባ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው የፍሎሪዳ ግዛትን ማጥቃት የሚችል ድሮን አግኝታለች የሚል ዘገባን ተከትሎ አሜሪካ ወታደራዊ እርምጃ ለመውሰድ “ሐሰተኛ ምክንያቶችን” እያደራጀች ነው ሲሉ ከሰሱ።

    ብሩኖ ሮድሪጌዝ የአሜሪካ የዜና ድረገጽ አክሲዮስ ዘገባን ተከትሎ ሃቫና “አትፈራም እንዲሁም ጦርነት አትፈልግም” ሲሉ ተናግረዋል።

    አክሲዮስ ምሥጢራዊ የደኅንነት መረጃዎችን ጠቅሶ ኩባ በአቅራቢያዋ የሚገኙ የአሜሪካ ዒላማዎችን ማጥቃት የሚችሉ 300 ድሮኖች ታጥቃለች ሲል ዘግቧል።

    አሜሪካ ኩባን “ለስምምነት እንድትቀመጥ” ለማስገደድ በሚል ወደ ግዛቷ የሚሄድን ነዳጅ ካገደች በኋላ አገሪቱ ከፍተኛ የነዳጅ እጥረት ገጥሟታል።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት የኩባ ኮሚኒስት አመራሮችን የቬንዙዌላ ፕሬዝዳንት ማዱሮን ለመያዝ የወሰዱትን ወታደራዊ እርምጃ ዓይነት እንደሚጠብቃቸው አስጠንቅቀዋል።

    ኩባ ድሮኖችን በመጠቀም በካሪቢያን ደሴት ላይ የሚገኘውን የአሜሪካ ወታደራዊ የጦር ሠፈር፣ ጓንታናሞ ቤይን እንዲሁም የባሕር ኃይል መርከቦችን እና ፍሎሪዳ ከተማን የማጥቃት ፍላጎት እንዳላት አክሲዮስ እሁድ ዕለት ዘግቧል።

    ዘገባው የአሜሪካ የደኅንነት ባለሥልጣንን ጠቅሶ የኢራን ወታደራዊ አማካሪዎች በሃቫና ይገኛሉ ያለ ሲሆን፣ ይህም ለአሜሪካ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት ሰበብ ሊሆን ይችላል ተብሏል።

    ሮድሪጌዝ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ "ምንም ዓይነት ቅቡልነት የሌለው ማስረጃ፣ የአሜሪካ መንግሥት ከቀን ወደ ቀን በኩባ ሕዝብ ላይ እያካሄደ ላለው ከባድ የኢኮኖሚ ጦርነት እና ለሚከፍተው ወታደራዊ ጥቃት ሐሰተኛ ምክንያቶችን እያደራጀ ነው" ሲሉ ጽፈዋል።

    “የተለዩ የመገናኛ ብዙኃን የአሜሪካ መንግሥት ጎጂ ውንጀላዎችን በማሠራጨት ረገድ ድጋፍ እያደረጉ ነው።”

    አክለውም ኩባ ጦርነት የማትፈልግ ብትሆንም ራሷን “ከውጭ ወረራ” ለመከላከል እየተዘጋጀች ነው ብለዋል።

    ሃቫና ለበርካታ ወራት ከአሜሪካ ጋር ያላትን ልዩነት ለመፍታት ንግግሮችን እያደረገች ነው። በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ከሩሲያ እንዲገባ የተደረገ ነዳጅ እያለቀ መሆኑ ተዘግቧል።

    ኩባውያን በከፍተኛ የነዳጅ እጥረት ምክንያት የኃይል መቆራረጥ ያጋጠማቸው ሲሆን፣ በዚህም የተነሳ የሕዝብ ትራንስፖርት፣ የውሃ ማሠራጫዎች፣ የቆሻሻ ማስወገጃዎች እንዲሁም ሆስፒታሎች ሥራቸውን ለማቋረጥ እየተገደዱ ነው።

  3. የሳዑዲ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከኢትዮጵያው ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር ተወያዩ

    የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ እና የሳዑዲ አረቢያ ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በአዲስ አበባ ተገናኝተው ተወያዩ።

    ሰኞ ዕለት ግንቦት 10 2018 ዓ.ም. ሁለቱ ሚኒስትሮች በሁለትዮሽ ጉዳዮች እና በቀጣናው ባላቸው የጋራ ፍላጎት ዙሪያ መወያየታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በማኅበራዊ ድረገጹ ላይ አስታውቋል።

    በተጨማሪም ባለሥልጣናቱ ከፖለቲካ እና ከፀጥታ ጉዳዮች ባሻገር፣ በሁለቱ አገራት መካከል ባለው ግንኙነት፣ ሕጋዊ የሠራተኛ ስምሪት ላይ መወያየታቸው ተገልጿል።

    በቀጣናዊ ሰላም እና ደኅንነት ዙሪያ የተወያዩት ሁለቱ ሚኒስትሮች በአካባቢው ላሉ የተለያዩ ግጭቶች ብቸኛው መፍትሔ በውይይት ፖለቲካዊ መፍትሄ መፈለግ መሆኑን መነጋገራቸውን ሚኒስቴሩ አስታውቋል።

    ምክትል የሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢንጂነር ዋሊድ አብዱልከሪም አል ካሪጅ በየካቲት ወር አሥመራን ከጎበኙ በኋላ ወደ አዲስ አበባ መጥተው ነበር።

    ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በሦስተኛ ወራቸው ወደ አዲስ አበባ የተመለሱ ሲሆን፣ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቴዎስ ጋር በሁለቱ አገራት የረዥም ጊዜ ወዳጅነት እና የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር ዙሪያ ተወያይተዋል።

    ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ የአገራቱ ግንኙነትን በማጠናከር በሳዑዲ አረቢያ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ደኅንነት መጠበቅ እንዲሁም ለኢትዮጵያውያን ሠራተኞች ሕጋዊ የሥራ ቅጥር እንዲመቻች መጠየቃቸው ተገልጿል።

    በሳዑዲ አረቢያ ከ200 የሚበልጡ ኢትዮጵያውያን በደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል በሚገኝ እስር ቤት የሞት ቅጣት እንደተፈረደባቸው እና ሌሎች 65 የሚሆኑ ስደተኞችም ተመሳሳይ ፍርድ እንደሚጠብቃቸው የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች አስታውቀዋል።

    ኢንጂነር ዋሊድ አብዱልከሪም አል ካሪጅ በበኩላቸው ለኢትዮጵያውያን ሠራተኞች ደኅንነቱ የተጠበቀ የሥራ ዕድል ለማረጋገጥ ሕጋዊ የሠራተኛ ቅጥር አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል።

    በተጨማሪም አገራቱ በጋራ ጉዳዮች ላይ ተመሳሳይ አመለካከት እንዳላቸው በመግለጽ፣ በመካከላቸው ያለውን ግንኙነት ለሁለቱ አገራት ጥቅም በሚያመጣ መልኩ መጠናከሩ አስፈላጊ መሆኑን አመልክተዋል።

    የሳዑዲ አረቢያው ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አገራቸው ከኢትዮጵያና ከሕዝቦቿ ጋር ያላትንታሪካዊ እና የረጅም ዘመን ግንኙነት እጅግ እንደምታከብር መግለጻቸውን የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያሠራጨው መረጃ አመልክቷል።

  4. ቢያንስ 6 አሜሪካውያን በኮንጎ ለተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ መጋለጣቸውን ተዘገበ

    በዴሞክራቲክ ኮንጎ በተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ ስድስት አሜሪካውያን ለቫይረሱ ተጋልጠዋል ሲሉ ምንጮች በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ተናገሩ።

    የዓለም የጤና ድርጅት ወረርሽኙን አሳሳቢ ዓለም አቀፍ የሕብረተሰብ ጤና አደጋ መሆኑን አውጇል።

    የዲሞክራቲክ ኮንጎ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር 350 የሚጠጉ ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው እንደተጠረጠረ እና 91 ሰዎች ደግሞ መሞታቸውን ዘግቧል።

    አንድ አሜሪካዊ የበሽታው ምልክቶች እንደታዩበት የተገለጸ ሲሆን፣ ሌሎች ሦስት ደግሞ ከፍተኛ ተጋላጭነት ወይም ንክኪ አላቸው ተብሏል።

    የአሜሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ ማዕከል (ሲዲሲ) "በቀጥታ የተጎዱ ጥቂት አሜሪካውያንን ደኅንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ ለቅቀው እንዲወጡ" ለማድረግ ድጋፍ እንደሚያደርግ ቢገልጽም ምን ያህል አሜሪካውያን እንደሆኑ ግን አላረጋገጠም።

    የአሁኑ የኢቦላ ዝርያ የሚከሰተው በቡንዲቡግዮ ቫይረስ ሲሆን፣ ለዚህም ምንም ዓይነት የተረጋገጡ መድኃኒቶች ወይም ክትባቶች የለም።

    በኡጋንዳ ሁለት ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸውሲረጋገጥ፣ አንድ ደግሞ መሞቱን የሲዲሲ አፍሪካ ዘገባ አመልክቷል።

    የአሜሪካ መንግሥት በዲሞክራቲክ ኮንጎ ለሚገኙት ዜጎቹ ደኅንነቱ ወደ ተጠበቀ የለይቶ ማቆያ ስፍራ ለማጓጓዝ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አንድ ምንጭ ለስታት የጤና ድረገጽ ተናግረዋል።

    በተጨማሪም አሜሪካውያኑ ጀርመን ወደሚገኝ የአሜሪካ ወታደራዊ ጣቢያ ሊወሰዱ እንደሚችል ድረ ገጹ ዘግቧል።

    የዓለም ጤና ድርጅት ዴሞክራቲክ ኮንጎ እና ኡጋንዳ ወረርሽኙን ለመከታተል፣ በበሽታው ከተያዙ ሰዎች ጋር ንክኪ ያላቸውን ለመለየት እና የመከላከያ እርምጃዎችን ለመተግበር የሚያስችሉ የአስቸኳይ ጊዜ ማዕከላትን እንዲያቋቁሙ መክሯል።

    ሥርጭቱን ለመግታት እንዲቻል በበሽታው መያዛቸው የተረጋገጠ ሰዎች፤ በ48 ሰዓታት ልዩነት በሚደረጉ ሁለት የቫይረሱ ምርመራዎች ነፃ መሆናቸው እስከሚረጋገጥ ድረስ ወዲያውኑ ለብቻ ሊለዩ እና ሕክምና ሊደረግላቸው እንደሚገባ ተቋሙ ገልጿል።

    በሽታው መከሰቱ የተረጋገጠባቸውን አገራት የሚያዋስኑ ጎረቤት መንግሥታት የቅኝት እና የጤና ሪፖርት ሥራቸውን እንዲያጠናክሩም ተነግሯቸዋል።

  5. ኢራን ለአሜሪካ አዲስ የሰላም ዕቅድ በፓኪስታን በኩል ማቅረቧ ተነገረ

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚካሄደውን ጦርነት ያስቆማል የተባለ ኢራን ያቀረበችውን አዲስ ዕቅድ ፓኪስታን ለአሜሪካ መስጠቷን ምንጮች ለሮይተርስ ተናገሩ።

    በሁለቱ አገራት መካከል እየተካሄደ ያለው የሰላም ድርድር ውጤት ሳያስገኝ በእንጥልጥል ባለበት ወቅት ዛሬ ሰኞ ነው ፓኪስታን የኢራንን አዲስ ዕቅድ ለአሜሪካ ያቀረበችው።

    ምንጮች በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ልዩነት በዚህኛው የሰላም ዕቅድ ማጥበብ ይቻል እንደሆነ ተጠይቀው “ጊዜ የለንም” ብለዋል፤ አክለውም ሁለቱም አገራት “የሚፈልጉትን በየጊዜው ይቀያይራሉ” በማለት ከስምምነት ያልተደረሰበትን ምክንያት ጠቅሰዋል።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አገራቸው ዩራኒየም የማበልጸግ መብቷ “ድርድር የሚደረግበት ወይም ከአቋም ፈቀቅ የሚባልበት ጉዳይ” እንዳልሆነ የተናገሩት ዛሬ ነበር።

    "በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው፤ ዩራኒየም የማበልጸግ መብት ለድርድር የሚቀርብ ወይም የሚለወጥ አይደለም። ኢራን ዩራኒየም ለማበልጸግ ያላት መብት የኒውክሌር መሣሪያዎች ላለማስፋፋት በተፈረመው ስምምነት መሠረት ዕውቅና የተሰጠው ነው" ብለዋል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው የኢራን ባለሥልጣናት ከስምምነት ለመድረስ መፍጠን እንዳለባቸው በመግለጽ “ጊዜው እየተገባደደ ነው” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ትራምፕ ማስጠንቀቂያውን የሰጡት ከእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጋር ትናንት እሑድ በስልክ መነጋገራቸውን ተከትሎ ነው።

  6. ኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብቷ ላይ “እንደማትደራደር ወይም ከአቋሟ ፈቀቅ እንደማትል” ገለጸች

    የኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብት “ድርድር የሚደረግበት ወይም ከአቋም ፈቀቅ የሚባልበት ጉዳይ” እንዳልሆነ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ተናገሩ።

    ቃል አቀባዩ ኢስማኢል ባቃኢ ዛሬ ሰኞ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ጦርነቱን ለመቋጨት በፓኪስታን አማካኝነት የሚደረገው ንግግር መቀጠሉን ገልጸዋል።

    ኢራን ባለ 14 ነጥብ የስምምነት ዕቅድ ወደ አሜሪካ ልካ እንደነበር ያስታወሱት ቃል አቀባዩ፤ ዋሽንግተንም ሆነ ቴህራን በዕቅዱ ላይ የራሳቸውን ሐሳብ ማንሳታቸውን ተናግረዋል።

    “የአሜሪካው ወገን ይህ [ባለ 14 ነጥብ] ዕቅድ ውድቅ መደረጉን ባለፈው ሳምንት በይፋ ቢያስታውቅም፤ ያቀረቧቸው ነጥቦች እና የማስተካከያ አስተያየቶች ዝርዝር ግን በፓኪስታን አማካኝነት ደርሶናል” ብለዋል።

    “ዕቅዳችንን በላክን ማግስት ከሌላኛው ወገን የቀረቡ ተከታታይ ዕቅዶች ደርሰውናል። ዕቅዶቹ ባለፉት ጥቂት ቀናት ውስጥ የተገመገሙ ሲሆን የእኛ ምላሽም ቀርቧል። በፓኪስታን አማካኝነት የሚደረገው ድርድር ቀጥሏል" ሲሉም ንግግሩን የማስጀመር ሂደቱ ያለበትን አረስድተዋል።

    ይህም ቢሆን ግን ኢራን ዩራኒየም የማበልጸግ መብቷን ለድርድር እንደማታቀርብ ባቃኢ ተናግረዋል።

    "በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው፤ [ዩራኒየም የማበልጸግ] መብት ልንደራደርበት ወይም ከአቋም ፈቀቅ የምንልበት ጉዳይ አይደለም። ኢራን ዩራኒየም ለማበልጸግ ያላት መብት የኒውክሌር መሣሪያዎች ላለማስፋፋት በተፈረመው ስምምነት መሠረት እውቅና የተሰጠው ነው" ብለዋል።

    እንደ ቃል አቀባዩ ገለጻ ኢራን የምትፈልጋቸው የድርድር ነጥቦች በግልጽ ተቀምጠዋል። እንዳይንቀሳቀሱ የታገዱ የኢራን ሀብቶች መለቀቅን በማሳያነት ያነሱት ቃል አቀባዩ፤ "እናንተ እኛ [ለድርድር] ያስቀመጥነው ቅድመ ሁኔታ እንደሆነ ትናገራላችሁ፤ እኛ የመብት ጥያቄ እንደሆነ እንናገራለን” ብለዋል።

  7. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን ላይ ሊወሰዱ ስለሚችሉ ወታደራዊ አማራጮች ‘በሲቹዌሽን ሩም’ ሊሰበሰቡ መሆኑ ተዘገበ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ላይ ሊፈጸሙ ስለሚችሉ ወታደራዊ አማራጮች ለመወያየት ማክሰኞ ዕለት ከፍተኛ የብሔራዊ ደኅነት አመራሮቻቸውን ይሰበስባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ አክሲዮስ ዘገበ።

    የአሜሪካው የዜና ምንጭ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮችን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ፤ የፕሬዝዳንቱ የብሔራዊ ደኅንነት ቡድን አባላት ስለ ኢራን ለመወያየት ቅዳሜ ዕለትም ተሰብስበው ነበር።

    ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫምስ፣ የዋይት ሃውስ መልዕክተኛ ስቲፍ ዊትኮፍ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ እና የሲአይኤ ዳይሬክተር ጆን ራትክሊፍ ከተሰብሳቢዎቹ መካከል ነበሩ ተብሏል።

    ትራምፕ ለአክሲዮስ በሰጡት ቃለ መጠይቅ፤ ከኢራን ጋን ስምምነት ላይ ይደረሳል ብለው እንደሚያስቡ ተናግረዋል።

    የኢራን የድርድር ዕቅድ ላይ የሚደረገውን ማሻሻያ እየጠበቁ መሆኑን የተናገሩት ፕሬዝዳንቱ፤ ከቀናት በፊት ከቀረበው የተሻለ ይሆናል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉም ጠቅሰዋል። ለድርድሩ ቀነ ገደብ ከማስቀመጥ ግን ተቆጥበዋል።

    “ስምምነት መፈጸም እንፈልጋለን። እንዲሆኑ የምንፈልገው ቦታ ላይ አይደሉም። እዚያ መረድስ አለባቸው ወይም ክፉኛ ይመታሉ፤ ያንን ደግሞ አይፈልጉም” ብለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ከመጀመሪያው ዙር ድርድር በኋላ ንግግሩን ለማስቀጠል አልተገናኙም።

    አሸማጋይ ሆና እየተንቀሳቀሰች ያለቸው ፓኪስታን ቅዳሜ ዕለት የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሯን ወደ ቴህራን ልካ ነበር። ድርድሩን ለማስጀመር እሑድ ዕለትም ከኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጋር ሲነጋገሩ ነበር።

  8. የእስራኤል ጦር ከኢራን ጋር ለሚኖር ሌላ ዙር ጦርነት እየተዘጋጀ መሆኑ ተዘገበ

    እስራኤል በቀጣይ በኢራን ላይ ሊፈጸም በሚችለው ጥቃት ውስጥ ሠራዊቷ ከአሜሪካ ጎን እንዲሳተፍ ለማድረግ እየተዘጋጀች መሆኑን የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    ካን የተባለው ቴሌቪዥን ጣቢያ ስማቸው ያልተጠቀሰ የእስራኤል የደኅንነት ባለሥልጣንን ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው፤ አሜሪካ በኢራን ላይ አዲስ ጥቃት ከጀመረች እስራኤል በዘመቻው ውስጥ በመሳተፍ የኢራንን “የኃይል ማመንጫ መሠረተ ልማቶችን” ዒላማ ታደርጋለች ብለዋል።

    ይህ ዘገባ የተሰማው ፕሬዝዳንት ትራምፕ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ እሑድ ዕለት በስልክ ከተወያዩ እንዲሁም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ኢራን ከስምምነት ለመድረስ ያላት ጊዜ ወደ ማብቂያው እየተቃረበ መሆኑን ከገለጹ በኋላ ነው።

    ካን ቴሌቪዥን እንደዘገበው በእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር እና በአሜሪካው ፕሬዝዳንት መካከል የተደረገው የስልክ ውይይት ከግማሽ ሰዓት በላይ የቆየ ሲሆን፣ ከኢራን ጋር ሌላ ዙር ጦርነት ሊከሰት በሚችልበት ሁኔታ ላይ ተነገግረዋል።

    ሌላኛው የእስራኤል ቴሌቪዥን ቻናል 12 ደግሞ በሁለቱ መሪዎች መካከል የተደረገውን የስልክ ውይይት “ከኢራን ጋር ለሚደረግ አዲስ ጦርነት በሚደረግ ዝግጅት ጥላ ስር” መካሄዱን በመጥቀስ የእስራኤል ጦርም ለአዲስ ግጭት በሙሉ ተጠንቀቅ ላይ” መሆኑን ዘግቧል።

    በተጨማሪም ቻናል 13 የተባለው የእስራኤል ቴሌቪዥን ጣቢያ በርካታ የጭነት አውሮፕላኖች የጦር መሳሪያዎችን ይዘው ወደ እስራኤል መግባታቸውን ዘግቧል።

    ዘገባው ጨምሮም የጭነት አውሮፕላኖቹ ጀርመን ውስጥ ከሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ተነስተው ባለፉት 24 ሰዓተት ቴል አቪቭ ውስጥ አርፈዋል።

  9. ኩዌት እና ኳታር በሳዑዲ አረቢያ ላይ የተፈጸመውን የድሮን ጥቃት አወገዙ

    ኩዌት እና ኳታር በተናጠል ባወጧቸው መግለጫዎች፤ ከኢራቅ የአየር ክልል በመነሳት ሳዑዲ አረቢያ ላይ የተሰነዘረውን የድሮን ጥቃት አወገዙ።

    ኩዌት፤ ይህ ድርጊት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት በባሕረ ሰላጤው መሠረተ ልማቶች ለመጠበቅ ያሳለፈውን ውሳኔ የሚጥስ ነው ብላለች።

    ሳዑዲ አረቢያ ደኅንነቷን ለማስጠበቅ ለምትወስዳቸው እርምጃዎች ያላትን ድጋፍም ገልጻለች።

    ኳታር በበኩሏ ድርጊቱን "ተቀባይነት የሌለው ጥቃት" እና የሳዑዲን ሉዓላዊነት በግልጽ የጣሰ ስትል ገልጻዋለች።

    ሁለቱም አገራት ለሪያድ ያላቸውን ሙሉ አጋርነት የገለጹ ሲሆን፤ ሳዑዲ ግዛቷን እና ዜጎቿን ለመጠበቅ የምትወስዳቸውን ማናቸውንም እርምጃዎች እንደሚደግፉ አስታውቀዋል።

    ኳታር እና ኩዌት መግለጫ ያወጡት ሳዑዲ አረቢያ የአየር መከላከያ ሥርዓቶቿ ሦስት የጥቃት ድሮኖችን መትተው መጣላቸውን ካስታወቀች በኋላ ነው።

  10. የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የኒውክሌር ጣቢያ አቅራቢያ ጥቃት መፈጸሙ ተገለጸ

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እሑድ ዕለት የኒውክሌር ኃይል ማመንጫዋ አቅራቢያ የተፈጸመው የድሮን ጥቃት እሳት እንዲነሳ ማድረጉን አስታወቀች።

    ክስተቱን “አደገኛ [የግጭት] መባባስ” ስትል የጠራችው ኤምሬቶች፤ ባለሥልጣናት ጥቃቱ ከየት እንደተፈጸመ እየመረመሩ መሆኑን ገልጻለች።

    የአገሪቱ መከላከያ ሚኒስቴር እንደገለጸው ድሮኖች ወደ ኤምሬቶች ግዛት የገቡት “በምዕራብ የድንበር አቅጣጫ" በኩል ነው።

    ሁለቱ ድሮኖች እንደተጠለፉ እና ሦስተኛው ግን በአቡ ዳቢ የሚገኘው የባራካህ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ "ከውስጣዊው ቅጥር ግቢ ይዞታ ውጭ" የሚገኝ የኤሌክትሪክ ጄነሬተርን እንደመታ ተገልጿል። እሳቱም የተነሳው በዚሁ ምክንያት ነው ተብሏል።

    በጥቃቱ ጉዳት አለመድረሱን የሚናገሩት ባለሥልጣናቱ፤ በአካባቢው የራዲዮሎጂካል ደኅንነት ደረጃ ላይም ተጽዕኖ አለማሳደሩን ገልጸዋል።

    የኤምሬቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ክስተቱን "ተቀባይነት የሌለው የጥቃት ድርጊት" በማለት ጠርቶታል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ለማንኛውም ጠበኛ ድርጊት ምላሽ የመስጠት መብት እንዳላት አስታውቋል።

    ሚኒስቴሩ "ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይል ተቋማትን ዒላማ ማድረግ ግልጽ የዓለም አቀፍ ሕግ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ስምምነት እና የሰብአዊ ሕግ መርሆዎች ጥሰት ነው" ብሏል።

    የኤምሬቶች መከላከያ ሚኒስቴር በበኩሉ "የአገሪቱን ደኅንነት ለማዳከም የሚደረጉ ማናቸውንም ሙከራዎች በጽናት እንደሚጋፈጥ" አስታውቋል።

    የአገሪቱ ባለሥልጣናት ድሮኑ ከየት እንደተተኮሰ እስካሁን አልገለጹም። ከዚህ ቀደም ግን ኤምሬቶች ከጦርነቱ መነሳት ወዲህ በነዳጅ እና በኢኮኖሚ መሠረተ ልማቶቿ ላይ ከተፈጸሙ ጥቃቶች ጀርባ ኢራን እንዳለች በመግለጽ በተደጋጋሚ ከስሳለች።

    የተባበሩት መንግሥታት የኒውክሌር ተቆጣጣሪ ተቋም ሁኔታውን በቅርበት እየተከታተለ መሆኑን ገልጿል። የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮሲ በክስተቱ “ከፍተኛ ስጋት” እንደገባቸው ተናግረዋል።

    ዋና ዳይሬክተሩ በዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ የኤክስ ገጽ በወጣው መግለጫቸው፤ "የኒውክሌር ደኅንነትን አደጋ ላይ የሚጥል ወታደራዊ እንቅስቃሴ ተቀባይነት የለውም" ብለዋል።

  11. ትራምፕ “ጊዜው እየተገባደደ ነው” ሲሉ ኢራንን አስጠነቀቁ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “ጊዜው እየተገባደደ ነው” ሲሉ ኢራንን አስጠነቀቁ።

    የሁለቱ አገራት የሰላም ንግግር እንደተቋረጠ ሲሆን፤ ትራምፕ “በአፋጣኝ እንቅስቃሴ ማድረግ አለባቸው፤ ካልሆነ አንዳች ነገራቸው እንኳ አይተርፍም” ብለው ዝተዋል። በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያቸው ላይ “ዋናው ነገር ጊዜ ነው” ብለዋል።

    ትራምፕ ማስጠንቀቂያውን የሰጡት ከእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ጋር ትናንት እሑድ በስልክ መነጋገራቸውን ተከትሎ ነው።

    ቴህራን ጦርነቱን ለማቆም ያቀረበችው የሰላም ዕቅድ ላይ አሜሪካ ከስምምነት መድረስ አለመቻሏን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ዋሽንግተን የሰላም ዕቅዱ ተቀባይነት እንዲኖረው ጥረት ካላደረገች ውጤት እንደማይገኝ የኢራኑ መህር የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ያሳለፍነው ሳምንት ትራምፕ የሁለቱ አገራት የተኩስ አቁም “በቋፍ ላይ ነው” ሲሉ ዘላቂነቱ አጠራጣሪ መሆኑን ገልጸዋል።

    የኢራን የሰላም ዕቅድ “ተቀባይነት የሌለው ነው” ብለው ትራምፕ ቢያጣጥሉም፤ የኢራን የውጭ ጉዳይ ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጊ “ምክንያታዊ እና ለጋስ” ነጥቦች እንዳቀረቡ ተናግረዋል።