
የፎቶው ባለመብት, CQ-Roll Call, Inc via Getty Images
አሜሪካ ለታይዋን ልትሸጥ የነበረውን 14 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የጦር መሣሪያ ለኢራን ጦርነት በቂ ክምችት
እንዳላት ለማረጋገጥ በሚል አቋረጠች።
የአሜሪካ የባህር ኃይል ተጠባባቂ ኃላፊ ሁንግ ካኦ ሐሙስ ዕለት የመረጃውን ትክክለኛነት ለሴኔቱ አባላት አረጋግጠዋል።
ይህ የአሜሪካ ውሳኔ የተሰማው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሽያጩን ለማጽደቅ ቁርጠኛ እንዳልሆኑ እና በጉዳዩ
ላይ ከታይዋን ፕሬዝዳንት ጋር እንደሚነጋገሩ ከገለጹ ከቀናት በኋላ ነው።
የታይዋን ፕሬዚዳንት ቢሮ ቃል አቀባይ አርብ ዕለት ለጋዜጠኞች "አሜሪካ በጦር መሳሪያ ሽያጭ ላይ ስላደረገችው ማስተካከያዎች" ምንም ዓይነት መረጃ እንዳልደረሳቸው
ተናግረዋል።
አሜሪካ ለታይዋን የምትሸጠው የጦር መሣሪያ ቤይጂንግን ለረዥም ጊዜ ሲያስቆጣት ነበር።
ካኦ ሐሙስ ዕለት በሴኔት ፊት ቀርበው “አሁን ለኤፒክ ፊውሪ የሚያስፈልገንን መሣሪያ፣ ምንም እንኳ በቂ ቢኖረንም፣ ለማረጋገጥ ለተወሰነ ጊዜ አቁመነዋል” ሲሉ አስረድተዋል።
ካኦ የጦር መሣሪያ ሽያጭን በተመለከተ "ከታይዋን ጋር አልተነጋገርኩም" ብለዋል።
አክለውም "ሁሉም ነገር እንዳለን እያረጋገጥን ነው፣ ነገር ግን አስተዳደሩ አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው ለውጭ አገራት የሚደረገው የመሣሪያ ሽያጭ ይቀጥላል" ብለዋል።
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለፎክስ ኒውስ ባለፈው ሳምንት "ከቻይና ጋር ለመደራደር ጥሩ ነጥብ ነው” ቢሉም የመሣሪያ ሽያጩ እንዲቆም መወሰናቸውን ግን እስካሁን አላረጋገጡም።
በተጨማሪም ለጋዜጠኞች
"በሚቀጥሉት አጭር ጊዜያት ውስጥ ውሳኔ ላይ እንደርሳለን" ሲሉ
ተናግረዋል።
እነዚህ አስተያየቶች የተሰጡት ፕሬዚዳንቱ ቤይጂንግ ደርሰው ከመጡ በኋላ ነው።
ትራምፕ ከዢ ጂንፒንግ ጋር ባደረጉት ውይይት ታይዋን በአሜሪካ እና በቻይና መካከል በጣም ወሳኝ ጉዳይ እንደሆነች ተናግረው ነበር።
ትራምፕ በኋላ ላይ ለጋዜጠኞች ከዢ ጋር የአሜሪካ የጦር መሣሪያ ሽያጭን በሚመለከት "በዝርዝር" መወያየታቸውን ተናግረዋል።
እንደ አውሮፓውያኑ በ1982 አሜሪካ ለታይዋን በጉዳዩ ላይ ቤይጂንግን ላለማማከር ቃል ገብታ ነበር።
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ስለ ጦር መሣሪያ ሽያጭ ከታይዋን ፕሬዝዳንት ላይ ቺንግ-ቲ ጋር ሊነጋገሩ መሆኑን ተናግረዋል
ዋሽንግተን ለቻይና መንግሥት እውቅና በመስጠት ከታይዋን ጋር ያላትን ይፋዊ ግንኙት ካቋረጠችበት የአውሮፓውያኑ 1979 ወዲህ የአሜሪካ እና ታይዋን መሪዎች በቀጥታ ተነጋግረው አያውቁም።
ቻይና ታይዋንን የግዛቷ አካል አድርጋ የምታይ ሲሆን፤ ከአንድነትን ለማምጣት ልትከተል ከምትችላቸው አማራጮች መካከል አንዱም በኃይል መጠቅለል ነው።