ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ላይ ጦርነት የማካሄድ ሥልጣናቸው በምክር ቤት በመገደቡ ቁጣቸውን ገለጹ

የፎቶው ባለመብት, EPA
የአሜሪካ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በኢራን ላይ ጦርነት የማካሄድ ሥልጣናቸውን የሚገድብ ውሳኔ በማሳለፉቸው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የምክር ቤቱን አባላት አጥብቀው ተቹ።
ፕሬዝዳንቱ ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለማብቃት የሚያስችለው ድርድር “ከመጨረሻ ደረጃ” ላይ በደረሰበት ጊዜ የአሜሪካ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጦርነት በማካሄድ ሥልጣናቸው ላይ ገደብ መጣሉን “አገር ወዳድነት አይደለም” ሲሉ ተናግረዋል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ በትሩዝ የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ውሳኔውን በተመለከተ ባሰፈሩት ጽሁፍ ተቀናቃኞቸቻውን ዲሞክራቶች እና እነሱን ደግፈው ድምጽ የሰጡ የፓርቲያቸው ሪፐብሊካን የምክር ቤት አባላትን ወቅሰዋል።
". . .ከኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ጋር የሚደረገውን ጦርነት ለማብቃት በመጨረሻው ድርድር መካከል ላይ እያለሁ አራት የሪፐብሊካን እና ሁሉም የዲሞክራቲክ ፓርቲ አባላት የምክር ቤት እንደራሴዎች ጦርነት የማካሄድ ሥልጣኔን የሚገድብ ትርጉም የለሽ ውሳኔ አሳልፈዋል” ብለዋል።
"ድርድሩ ከምን ደረጃ ላይ እንዳለ እያወቁ እንዴት እንዲህ ያለ ከአርበኝነት የራቀ ውሳኔ ይሰጣሉ?” ሲሉ በተወካዮች ምክር ቤት አባላቱ ውሳኔ ደስተኛ አለመሆናቸውን ገልጸዋል።
ከዚህ ቀደም ብዙም ባልታየ ሁኔታ የአሜሪካ ምር ቤት ረቡዕ ዕለት የዲሞክራቲክ ፓርቲ አባላት ያቀረቡትን ፕሬዝዳንት ትራምፕ በኢራን ላይ የሚያካሂዱትን ጦርነት የሚገድብ የውሳኔ ሀሳብ በመደገፍ ድምጽ ሰጥተዋል።
ይህ ውሳኔ በምክር ቤቱ ውስጥ ካሉ ዲሞክራቶች የ211 አባላት ድጋፍ ያገኘ ሲሆን፣ አራት የትራምፕ ፓርቲ አባላትም ደፈግወውት በ215 ለ208 በሆነ የድምጽ ብልጫ ነው ተቀባይነት ያገኘው።
የኢራን ጦርነት ከተጀመረ በኋላ የትራምፕን ጦርነት የማካሄድ ሥልጣን ለመገደብ በተደጋጋሚ ድምጽ ቢሰጥም ተቀባይነት ሳያገን ቀርቶ ነበር። አሁን ግን አብዛኞቹ ሪፐብሊካኖች ውሳኔውን ቢቃወሙትም በአብላጭ ድምጽ አልፏል።






















